የህወሃት/ኢህአዴግ የሃይል መንገድ የሚያሳየን ድርጅቱ የሐሳብ ምክነት እንዳለበት ነው በአንድነት ፓርቲ የሶስት ወራት ህዝባዊ ንቅናቄ ላይ መሳተፍ መቻሌ አገሪቱን በመምራት ላይ ስለሚገኘው ጡንቸኛው ድርጅት ብዙ ነገሮችን በቅርበት ለማወቅ አስችሎኛል፡፡
ወደ ደቡብ ክልል በማቅናት በወላይታ ህዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ የከፈልነው መስዋዕትነት መሪዎቻችን ምን ያህል የፓርቲዎችን ከህዝብ ጋር መገናኘት እንደሚፈሩ እንዳውቅ አድርጎኛል፡፡ ሹፌራችን ምንም በማያውቀው መንገድ ‹‹ፖለቲከኞቹን ወደዚህ ያመጣህው አንተ ነህ ››ተብሎ ተደብድቧል፣ጄኔሬተር የሸጠልን ነጋዴ ከሁለት መቶ ሜትር በላይ በሩጫ ተከትሎን እንደ ህጻን በሁለት ጉንጮቹ መንታ መንታ እያነባ የሸጠልንን ጄኔሬተር እንድንመልስለት ይህንን ባናደርግ ግን ንግዱ ተዘግቶ ልጆቹ እንደሚበተኑ ተማጽኖናል፡፡ታርጋ ባልለጠፈ ሞተር ሳይክል እላዬ ላይ ሊከመር ከነበረ ባለ ሞተር ያመለጥኩትም ሱቅ ውስጥ ዘልዮ በመግባቴ ነበር፡፡የከተማውን ፖሊስ ጣብያ የሚመሩ ሻለቃ ‹‹ከአቅሜ በላይ የሆነ ነገር ሊፈጠር እንደሚችል መረጃ ደርሶኛል በፍጥነት ከተማውን መልቀቅ አለባችሁ›› በማለት በመኪናቸው በማጀብ ሸኝተውናል፡፡ እኛን በመተባበር ቅስቀሳ ላይ የተሰማሩ የአካባቢው ተወላጅ ዩኒቨርስቲ የሚማር ልጃቸው በምሽት ተጠልፎ ተወስዶባቸዋል፣በፍቼ ሁለት የአንድነት አባላት በአስራ ስድስት ሰዎች ተቀጥቅጠዋል፡፡አስገራሚው ነገር ይህንን ቅጥቀጣ የመሩት የአካባቢው የፍትህ ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑ ሰው ናቸው፡፡በሌሎቹም ቦታዎች እስራት፣ድብደባ፣ማስፈራሪያና ንብረት ቅሚያ በሽበሽ ነበር፡፡ ሰሞኑን በአረና አባላትና አመራሮች ላይ የደረሰው በደል ከላይ ለማስቀመጥ የሞከርኩትን ክስተት መለስ ብዬ እንዳስታውሰው አድርጎኛል፡፡የህወሃት ሰዎች የድርጅቱ መስራች የነበሩትን የእድሜ ባለጸጋ ከትግራይ ህዝብ ባህል ባፈነገጠ መልኩ አቶ አስገደን ደብድበዋል፣ ህወሃትም በዚህ ድርጊቱ ታሪኩን አራክሷል፡፡በማህበራዊ ድረ ገጾች የምናውቀው አብርሃ ደስታም ከድንጋይ አላመለጠም፡፡ እነዚህ ነገሮች ምን ይነግሩናል? በእኔ መመዘኛ ሰላማዊ ትግል አያዋጣም ለሚሉ ሰዎች ይህ ድርጊት ጥዑም ዜማ ሊሆናቸው አይችልም፡፡ይህ ድርጊት በግልጽ የሚነግረን ህወሃት/ኢህዴግ ሰላማዊ ትግልን ከመሳሪያ በላይ እንደሚፈራው፣የሰላማዊ ትግል ቋንቋ እንደ ባቢሎን ሰዎች ድብልቅልቅ እንደሆነበት ነው፡፡ ህወሃትን የትግራይ በማድረግ ህዝቡን በአንድ ጠርሙስ የከተትን ሰዎችም አረና ላይ የደረሰው ነገር ህወሃት በህዝቡ የተፈጠረ የህዝቡ ወኪልና ንብረትነቱም ለህዝቡ ሳይሆን ለራሱ ብቻ መቆሙን እንድንመለከት ያደረገ በመሆኑ በህወሃትና በትግራይ ህዝብ መካከል የሰማይና የምድር ያህል ርቀት መኖሩን መገንዘብ ይገባናል፡፡ ህወሃት/ኢህአዴግ በተቃዋሚዎቹ ላይ የሚሰነዝረው የሰለጠነ አስተሳሰብ የሌለው መሆኑን በመረዳትም ትግሉ የበለጠ የሚጠናከርበትን መንገድ ተቃዋሚዎች ተቀራርበው መዘየድ ይኖርባቸዋል፡፡ምን አልባት አረና ላይ የተወረወረው ደንጊያ ነገ ወደ መሳሪያ ሊለወጥ ይችላል፡፡ያ ካምፕ ያለው ይህ በመሆኑም ተቃዋሚዎች ለሚመጣው ሁሉ ዝግጁ መሆን ግድ ይላቸዋል፡፡ ለህወሃት/ኢህአዴግ ማዘን ይገባናል፣የድርጅቱ አባላትና አመራሮች ደግሞ ማፈር ይጠበቅባቸዋል፡፡ላለፉት 23 አመታት አገሪቱን የመራ ፓርቲ እንዴት እስካሁን በደደቢት ቋንቋ ይናገራል? ለድርጅቱ የምናዝነው ከመለስ ፊትና ኋላም ቢሆን ከምክነት ባለመዳኑ ጭምር ነው፡፡
No comments:
Post a Comment