
የፀረ ሽብር ግብረ ሃይሉ መላው ህብረተሰብና የፀጥታ ሃየሎች ሁኔታውን በንቃት በመከታተል ከፖሊስና የደህንነት ሃይሎች ጋር በትብብር እንዲሰሩም ጥሪውን አስተላለፏል፡፡
በጋራ የፀረ ሽብር ግብረ ሃይሉ የተላለፈው ይኸው መግለጫ ባለፈው ጥቅምት 3 ቀን 2006 ዓ.ም አዲስ አበባ ከተማ ቦሌ አካባቢ ለሽብር ተግባር ሲሰናዱ በራሳቸው ላይ ባደረሱት አደጋ ህይወታቸው የጠፋ ሁለት ሶማሊያዊያን አሸባሪዎች ጉዳይ ላይ ምርመራ ሲያደረግ መቆየቱን አስታውሷል፡፡
እነዚህ ሁለት አሸባሪዎች በወቀቱ የኢትዮጵያና የናይጀሪያ ብሄራዊ ቡድኖች የሚያደርጉትን የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ውድድር በሚከታተሉ የስፖርት አፍቃሪዎች ላይ አደጋ ለማድረስ ዓላማ እንደነበራቸው የሚያሳዩ መረጃዎች መገኘታቸውን መግለጫው በተጨማሪ አስታውቋል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ የፀረ ሽብር ግብረሃይሉ የጀመረውን ምርመራ በተጠናከረ መንገድ እያካሄደ መሆኑን ግብረሃይሉ ገልጿል፡፡
በቅርቡ በአዲስ አበባ እና በሌሎች የክልል ከተሞችና አካባቢዎች በሁለት አቅጣጫ የተመራና ተመሳሳይ ዓላማና ቅንጅት ያለው የሽብር ጥቃት ዝግጅት መኖሩን የሚመለከት አስተማማኝ መረጃ ማግኝቱን የፀረ ሽብር ግብረ ሃይሉ የመረጃ ክፍል ይፋ ባደረገው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የሽብር ጥቃት ዝግጅቶቹ ጠንሳሾች አሸባሪው የአልሸባብ ቡድን እና የኤርትራ መንግስት ያሰማራቸው አሸባሪዎች መሆናቸውን የፀረ ሽብር ግብረ ሃይሉ በመግለጫው አስታውቆ የአሸባሪዎች አላማም በሽብር ጥቃቶች የሀገሪቱን ሰላምና መረጋጋትን በማናጋት የልማት ግስጋሴዎችን ማደናቀፍ መሆኑን ነው የገለፀው፡፡
በህብርተሰቡ ላይ አሰቃቂ ጉዳት ሊያስከትል የሚችለውን ይህን እኩይ የሽብር ጥቃት ዝግጅት ተግባራዊ ሳይሆን ለማምከን በሚደረገው ጥረት ላይም መላው ህዝብና የፀጥታ ሀይሎች እንደወትሮው በመተባበር ንቁ ክትትልና ተሳትፎ በማድረግ የድርሻቸውን እንዲወጡም የፀረ ሽብር ግብር ሀይሉ አበክሮ ጠይቋል፡፡
በመሆኑም ህዝብ በሚዝናናባቸው ስፍራዎች የሚሰሩ ዜጎች ከወትሮው የተለየ አጠራጣሪ ሁኔታዎችና ግለሰቦች በገጠሟቸው ጊዜ በአካባቢያቸው ላሉ የፖሊስና የፀጥታ ሀይሎች በፍጥነት እንዲያሳውቁም የፀረ ሽብር ግብረ ሀይሉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በተጨማሪም ሆቴሎቻቸውንና መኖሪያ ቤታቸውን የሚያከራዩ ባለንብረቶችና ባለ ይዞታዎች በተለይ የውጭ ሀገር ዜጎችንና የማያውቋቸውን ኢትዮጵውያንን አድራሻ በአግባቡ መዝግበው በመያዝ መረጃን ለሚመለከተው አካል የማሳወቅ የህግ ግዴታ እንዳለባቸው መግለጫው በጥብቅ አስጠንቅቋል፡፡
በተመሳሳይ መኪናዎቻቸውን የሚያከራዩ ግለሰቦች፣ድርጅቶችና የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ባለታክሲዎች የደበኞቻቸውን ማንነት የሚገልጽ ሙሉ መረጃ የመያዝና የማሳወቅ እንዲሁም የሚጭኗቸውን ማናቸውንም ዕቃዎች የማወቅ ግዴታም ያለባቸው መሆኑን የፀረ ሽብር ግብረ ሀይሉ አስታውቋል፡፡ ህብረተሰቡ አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያጋጥመው ሁኔታውን በአቅራቢያው ላሉ የፖሊስና የፀጥታ ሀይሎች እንዲያሳውቅም ነው ያሳሰበው፡፡
በየአካባቢው በሚገኙ የፍተሻ ኬላዎች ላይ የሚሰሩ የፍተሻ ስራተኞች ተግባራቸውን ከወትሮ በተለየ ጥንቃቄ እና አትኩሮት ማከናወን እንዳለባቸውም የፀረ ሽብር ግብረ ሀይሉ ማስታወቁን የኢሬቴድ ዘግቧል፡፡
No comments:
Post a Comment